Thursday, April 15, 2010

አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ

የአባታችን የእስትንፋሰ ክርስቶስ የተወለዱበት ቦታ ዳውንት ፀውን ዓባይ ይባላል:በሰሜን በኩል የእናታቸው ሃገር ደብረ ድባ የቄርሎስ ቦታ ይባላል:የአባታቸውም ሃገር የእግዚአብሄር አብ ደብር አጠገብ ዳውንት(ደብረ አስጋጅ)ይባላል:የአባታቸውም ስም መልዓከ ምክሩ ሲባሉ እናታቸው ደግሞ ወለተ ማርያም ይባላሉ:እነዚ ባል እና ሚስት በህግ ጸንተው የሚኖሩ እንደ ዘካሪያስ እና እንደ ኤልሳቤጥ መልካም ስራን በመስራት እግዚአብሄርን የሚያገለግሉ ነበሩ:ቀድመውም 2 ልጆችን ወልደው ነበር እና ከዛም እመቤታችንን የተባረከ እግዚአብሄርን የሚያገለግል በጸሎቱ ሰውን የሚጠቅም ልጅ እንድትሰጣቸው ዘወትር ይለምኑአት ነበር: እግዚአብሄርም ፀሎታቸውን ሰምቶ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሚያዚያ 8 ተፀነሱ እና ታህሳስ 8 ቀን ተወለዱ:ልክ በተወለዱ እለትም ተነስተው በግራቸው ቆመው 3 ግዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስቅዱስ ብለው አመሰገኑ:9 ግዜም ሰግዱ:ከዚህም በሁአላ በ40 ቀናቸው ጥምቀትን ተጠምቀው ስማቸውም እስትንፋሰ ክርስቶስ ተባለ:ከዛም ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸው አደጉና አባትየው ዋሻ ውስጥ 60 አመት ወደ ኖረ ቅዱስ ኪራኮስ ወደ ሚባል አባት ወሰደው ትምህርት እንዲያስተምረው ለመኑት:ከዛም ፃድቁ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ በአባ ኪራኮስ ተመርቆ ትምህርቱን ጀመረና እንደሌላው ሰው ጊዜ አልፈጀበትም:ወዲአው ይረዳ ነበር ከዛም ፃድቁ አባታችን የተለያዩ የሃይማኖት ትምህርቶችን በፍጥነት ተማረ ከዛም በክርስቶስ ፍቅር በእመቤታችን ፍቅር ልቡ ደማ:በውስጥ በአፍአ ድንግል ስትሆን የህያው የእግዚአብሄር አብ የባህርይ ልጅ ወልድን በጡቶቹአ ወተት አጥብታ ያሳደገችው በሁለት ወገን ድንግል የምትሆን መልካሚቱአ እርግብ እመቤታችን ጽጌ የሚባል ልጁአን እንደምትስም እንዲሁ ጻድቁ አባታችንን ትስመው ነበር:ከዛም አባታችን በመንፈሳዊ ተጋድሎ ቅኑት እንደገበሬ ፅሙድ እንደበሬ ሆኖ ሳይመነኩስ የምንኩስናን ስራ መስራት ጀመረ:እንደ እሳት ወላፈን ፈጥኖ የሚያልፍ የዚን አለም ጣዕም በመናቅ ህሊናው እንደ እሳት ነደደ አንደበቱም 46ቱን ብሉያትን 35ቱን ሃዲሳትን መጽሃፍ አንባቢ አደረገው ከዚህም ሌላ ቅዱሳት መጽሃፍትን:-150ውን መዝሙረ ዳዊት,ድርሳናትን ውዳሴ ማርያምን,የጻድቃን እና የሰማእታትን መልክአ,አስራ ስምንቱን ተአምረ ማርያም,ተአምረ እየሱስ,የሰኔ ጎሎጎታ,ልፋፈ ጽድቅ,እቀበኒ ክርስቶስ,7ቱ ኪዳናትን,ባርቶስ,እና ገድለ አቡነ ኪሮስ,ጊዮርጊስ,ኤዎስጣቴዎስ,ገብረ መንፈስቅዱስ,ተሰአቱ ቅዱሳን እንዲሁም ሰይፈ ሲላሴን እና ሰይፈ መለኮትን እንዲሁም ሌሎችን ቅዱሳን መጽሃፍቶችን ዘወትር አብዝቶ ይፀልይ ነበር:ጻድቁ አባታችን ጾምና ጸሎትን ትዕግስት አርምሞ ልጉአም ሆኑለት:እግሮቹ በሐዋርያት ወንጌል ጭንጫ ላይ ቆሙ:ቅድስት ንጽህት ድንግል በምትሆን በእመቤታችን በማርያም ፍቅር ገመድ ተጎተተ:የአሸናፊ የእግዚአብሄር ስሙን በመፍራት ሰውነቱን ይገስጻል:በጻድቃን እና በሰማእታት ጎዳና ሰውነቱን ያሮጠዋል:ከዛም አባ ኪራኮስ አባታችንን መርቆ ወደ አባቱ ሰደደው:ከዛም አባትየው ስሙ ማርቆስ ወደሚባል ጳጳስ ክህነት ይሰጠው ዘንድ ወሰደው ከዛም ጳጳሱ ባርኮ ዲቁና ሾመው እና ወደ ሃገራቸው ዳውንት ተመለሱ:ከዛም በእመቤታችን እና በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በድቁና ያገለግል ጀመር አባቱን እና እናቱንም በማገልገል እስከ 14 አመቱ ድረስ ተቀመጠ በሁአላም በ 14 አመቱ አለምን ንቆ ይመንን ዘንድ ለቤተሰቦቹ ነገራቸው አባቱም ቤተ ክርስቲያን ሄዶ አልቅሶ ቢጸልይ "ይመነኩስ ዘንድ ይሂድ ስልጣኑ እስከ ሰማይ ከፍ ከፍ ይላል ስም አጠራሩ እስከ አለም ዳርቻ ይደርሳል"የሚል ቃል ከሰማይ ሰማና በፍቅርና በሰላም አሰናበቱት:ከዛም አባታችን በ14 አመቱ ብዙ ገዳማትን እየጎበኘ ወደ ደብረ ሃይቅ አቡነ ኢየሱስ ሞአ ደረሰ:ከዛም እንደገዳም ስርአት 3 አመት ተፈተነና ከዛም ምንኩስናን ለበሰ ከዛም ከብዙ ተጋድሎ በሁአላ ድቁና ወደ ሾመው ጳጳስ ሄዶ ቅስናን ተቀበለ ከጥቂት ቀንም በሁአላ ቁምስናን እና ኤጲስቆጶስነትንም ሾመው:ከዛም አባታችን "ጌታችን ሰውነቱን በገራህተ መስቀል የጣለ ነፍሱን ያገኛታል:ስለኔ ሰውነቱን በገራህተ መስቀል ይጣል"ያለውን አስቦ በጾም በጸሎት በትርህምት በስግደት ኖረ:ከዛም እንደ 12 ሃዋርያት አጋንንትን እያወጣ:ድውያንን ይፈውስ ለምጻምን ያነጻ ጀመር:ከዛም የአባታችን ተአምር በምድረ ኢትዮጵያ ተሰማ ህዝቡም እሱን ያይ ዘንድ ካለበት ይመጣል:ከዛም አባታችን ኢትዮጵያን እየተዘዋወረ ያስተምር ይጸልይ ጀመር በሁአላም በ33 አመቱ ወደ ደብረ ድባ መቶ ሚያዚያ 9 ቀን ምንኩስናን ተቀበለ በዚያች ቀንም አስኬማን,ቅናትን,ቀሚስን,መታጠቂያን,መስቀልን,በትርን ጭራንና ስእልን ተቀብሎ ሲጸልይ ዋለ:ከዛም እንዳስለመደው በየ ሃገሩ እየተዘዋወረ እያስተማረና ድውይን እየፈወሰ ሃገሪቱአን አቀና በየግዜውም የሚነሱ ንጉሶች ይመጡና ከአባታችን ዘንድ ይባረኩ ነበር:ብዙ ልጆችም አፍርቶ ነበር በስተመጨረሻም ጌታችን ከእናቱ እና ከብዙ ቅዱሳን ጋር ሆኖ ወደ አባታችን መቶ ብዙ ቃል ኪዳን ሰቱአቸዋል በስተመጨረሻም አባታችን አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ በ ሚያዚያ 9 ቀን አርፉ:: የአባታችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ረድኤት እና በረከት አይለየን አሜን!!!!! ምንጭ ገድለ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ

No comments:

Post a Comment