Friday, August 6, 2010

ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ክፍል 1

1:- አኮቴተ ቁርባን ዘእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ ዘደርሰ በመንፈስቅዱስ አባ ሕርያቆስ ኤጲስ ቆጶስ ዘሃገረ ብህንሳ ጸሎታ ወበረከታ የሃሉ ምስለ ኩሎሙ ህዝበ ክርስቲያን ለዓለመ ዓለም አሜን ::
ሕርያቆስ ማለት ህሩይ ማለት ነው : ለሹመት መርጠውታልና: አንድም ረቂቅ ማለት ነው ምሥጢረ ሥላሴን ይናገራልና : ከሊቃውንትስ ምሥጢረ ሥልሴን የማይናገር የለም ብሎ ከሁሉ ይልቅ እሱ አምልቶ አስፍቶ አጉልቶ ይናገራልና አንድም ፀሐይ ማለት ነው: አብ ፀሐይ ወልድ ፀሐይ መንፈስቅዱስ ፀሐይ ብሎ ጽፏልና : አንድም ብርሃን ማለት ነው: የምዕመናንን ልቦና በትምህርቱ ብሩህ ያደርጋልና : ዘአብርሃ መንበረ ማርቆስ በብርሃን እንዲል :አንድም ንብ ማለት ነው: ንብ የማይቀምሰው አበባ የለመ እሱም የማይጠቅሰው ሊቅ የለም:ይህም እንደምን ነው ቢሉ:ሐዋርያት የተማረ ግብረ ገብ ይሾም ብለው ሥራት ሰርተዋል: ይህስ አይደለም ሁለቱን አስተባብሮ የያዘ አይገኝም ብሎ የተማረ ከሆነ ይሾም ብለዋል::በትምህርቱ መናፍቃንን ተከራክሮ ይመልሳልና ብለው ግብረ ገብም ከሆነ ይሾም ብለዋል:በጸሎቱ ይጠብቃል: በትሩፋቱ ያጸድቃል:ትምህርቱን ውሎ አድሮ ያደርገዋልና ብለው ሾሙት :ይህም አባ ህርያቆስ ያልተማረ ግብረ ገብ ነው :ቢማርም ለጸሎት ለቅዳሴ ያህል ነበር:በብህንሳ በ10000 መነኮሳት በ10000 መነኮሳይያት ተሹሟል በብዙም መሾም ልማድ ነው::
አባ ሆርና አባ ኤስድሮስ በ1000 አባ አሞን በ3000 አባ ጳኩሚስ በ6000 አባ ሰራብዮን በ10000 ተሾሙ:ይህችም ብህንሳ ቅድመ ትሰይም አርጋድያ ወድህረ መኑፍ ይላል: ብዙ ግዜ ስመ ተፋልሶ አግኝቷታል :በፊት አርጋድያ ኋላም መኑፍ ተብላለች ዛሬም ብህንሳ ትባላለች:ሴትና ወንድ ያልተለየባት ገዳም ናት:እንደ ዘጌ እንደ ቆራጣ እንደ ቀንጠፋሜ እርሱም ግብረ ገብ ነውና ሥራት ቢያጸናባቸው ይጣሉታል:ያልተማረ ነውና ይንቁታል: ከመጠምጠም መማር ይቅደም እንዲሉ ከመሾም መማር አይቀድምምን እያሉ; እሱ ግን ወእቀውም ዮም በትህትና ወበፍቅር ብሎ እንዲያመጣው: እንደጠሉኝ ልጥላቸው እንደ ናቁኝ ልናቃቸው ሳይል በፍቅር እና በትህትና ጸንቶ ያስተምራቸው ነበር::
ከዕለታት ባንዳቸው በምን ምክንያት እንሻረው አሉ:ቀድሰህ አቁርበን ብለን በዚህ ምክንያት እንሻረው ብለው መክረው ቀድሰህ አቁርበን አሉት: የሱ ግን ተምኔቱ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም የእመቤቴ ምስጋና እንደባህር አሸዋ እንደ ሰማይ ኮከብ በዝቶልኝ እንደምግብ ተመግበው እንደ መጠጥ ጠጥቼው እንደ ልብስ ለብሼው እያለ ይመኝ ነበር:ቅዳሴ ገብቶ ሥርዓቱን ጨርሶ ከፍሬ ቅዳሴው ሲደርስ ከሊቃውንት ቅዳሴ የሚያስቸግር የማንን እናውጣለት እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ የለመኗትን የማትነሳ የነገሯትን የማትረሳ እመቤት ገልጻለት ጐሥዓ ልብየ ቃለ ሠናየ ብሎ ወይእዜኒ ንሰብሐ እስኪል ድረስ ሰተት አድርጎ ተናግሮታል: የሚንቁት የሚጠሉት ይህ የነገሩትን ቀለም እንኳን አከናውኖ መናገር የማይችል ዛሬስ እንግዳ ድርሰት እደርሳለው ብሎ አገኝ አጣውን የቆጥ የባጡን ይቀባጥራል: ብለው አደነቁበት የሚወዱት የሚያከብሩት ከመንፈስቅዱስ ነው እንጂ እንዲ ያለ ምሥጢር ከእሩቅ ብዕሲ ይገኛልን ብለው አደነቁለት: ወዲያው የሚወዱት የሚያከብሩት ጽፈን ደጉሰን አንይዘውምን አሉ: የሚንቁት የሚጠሉት ደግሞ ማን ተናገረው ብለን እንይዘዋለን አሉ እንደ ሊማዱ አድርገን አንይዘውም አሉ:: ለሃገራቸው እንግዳ ድርሰት የተደረሰ እንደሆነ ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ይጥሉታል: ከእሳት ደህና የወጣ እንደሆነ ከውሃ ይጥሉታል ከውሃ የወጣ እንደሆነ ከህሙም ላይ ይጥሉታል ድውይ የፈወሰ እንደሆነ ደገኛ ድርሰት ነው ብለው ይይዙታል::
ይህንንም ቅዳሴ ማርያም ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ላይ ጣሉት ከእሳት ደህና ወጣ: ከውሃ ጣሉት ከውሃ ደህና ወጣ: ከህሙም ላይ ጣሉት ድውይ ፈወሰ: ይልቁንም ሙት አስነስቷል:: ደገኛ ድርሰት ነው ብለው ጽፈው ደጉሰው ይዘውታል:በጥራዝም 14ኛ አድርገው ጠርዘውታል: ከ14ቱ ቅዳሴም ተአምራት ያልተደረገበት የለም: የቀደሰበት ምን ቀን ነው ቢሉ: ከእመቤታችን ከ 33ቱ በዓላት ባንዱ ቀን ነው: አንድ ባህታዊ ከባለሟልነት የተነሳ ከ33ቱ በዓላት ማንን ትወጃለሽ ብሎ እመቤታችንን ጠየቃት:ኪዳነምህረትን ልደታን አስተርአዮን ፍልሰታን አለችው: ከሊህ ከ4ቱስ ማንን ትወጃለሽ ቢላት ከጸባብ ወደ ሰፊ: ከጨለማ ወደ ብርሃን: የወጣውበት ነውና ልደቴን እወዳለው አለችው: ቀድሞ እነ ሳልወለድ እናትና አባቴን መባችሁን አንቀበልም ብለው አዝነው ተክዘው ነበር: የነሱ ሃዘን ሃዘኔ ነውና እነን ከወለዱ በኋላ መባቸውን ተቀብለዋቸው ደስ ብሎዋቸዋል: የነሱ ደስታ ደስታዬ ነውና እንዳለችው የልደታ እለት ነው የቀደሰው:: እሱስ ማንን ሊቀድስ ኖሯል ቢሉ ከቅዳሴ ሐዋርያት ሌላ አያቅም ነበርና ቅዳሴ ሐዋርያትን: ይህስ አይደለም ለእመቤታችን ቅዳሴ ሐዋርያት ምኗ ነው: ምን ቢቸግር ተበድሮ ጋሬዳ እንዲሉ ቅዳሴ እግዚእን ሊቀድስ ነበር ስሟን ባያነሳ እምድንግል ተወሊዶ ከመ ፈቃድከ ይፈጽም ብሎ በምሥጢር ያነሳታል::
ከባህር ወዲህስ ማን አምጥቶልናል ቢሉቅዱስ ያሬድ ማይ ኪራህ መደባይ ታብር በሚባል ቦታ ይኖር ነበር እመቤታችን ቅዱስ ኤፍሬምን ከሶርያ አባ ሕርያቆስን ከብህንሳ በደመና ጠቅሳ ያረድ ካለበት አድርሳ አንተ ውዳሴየን አንተ ቅዳሴየን ነግራችሁት በዜማ ያድርስ ብላቸው እነሱም ነግረውት በዜማ አድርሶታል:: ከዚሁ አያይዞ 13ቱንም ቅዳሴ በዜማ ደርሷል: ይህም ሊታወቅ ሥረይ በቅዳሴ ማርያም ይበዛል::ከተከዜስ ወዲህ ማን አምጥቶልናል ቢሉ ሳሙኤል ትውልደ ጌዴዎን ዘገበዘ አክሱም ይለዋል እሱ አምጥቶልናል እሱም ይሄን እየደገመ ሲሄድ ክንድ ከስንዝር ከመረት መጥቆ ይሄድ ነበር: ከዕለታትም በአንዳቸው ውሃውን ቢባርከው ህብስት ሆኖለት ተመግቦ ምዕመናንን መግቧቸዋል:: እመቤታችንም የፍቅር ምልክት ሁለት ንዋያት ሰታዋለች ነጭ እጣን እና እንቁ ነው: ከዛም አያይዛ ውዳሴየን ከቅዳሴዬ ጋራ አንድ አድርጎ የሚደግመውን ሰው አንተ ከገባህበት ውሳጤ መንጦላዕት አገባዋለው:ብላ ተስፋውን ነግራዋለች:: ይሀውም ሊታወቅ ዛሬ በዋልድባ ያጠና በቃሉ: ያላጠና በመጽሃፍ ቅዳሴ ማርያም ሳይደግም የሚውል የለም:ይህም ተስፋ ውዳሴዋን ከቅዳሴዋ ጋር አንድ አድርጎ ለምደግም ሰው ሁሉ ነው:እንጂ ለሱ ብቻ አይደለም:ዳንድ ባህታዊ ከምስጋናሽ ሁሉ ማንን ትወጃለሽ ብሎ ቢጠይቃት ልጄ ዳዊትን አቡነ ዘበሰማያትን ቢደግሙለት እንዲወድ እኔም ውዳሴዬን ቅዳሴዬን ቢደግሙልኝ ወዳለው ብላዋለች ::
አባ ሕርያቆስ ተሹሞ ሳለ ብዙ ድርሳንን ደርሷል ብዙ ተግሳጽ ጽፏል ከብዙውም አንዱ ይህ ቅዳሴ ነው እረፍቱ በጥቅምት 2 ነው::
ልመናዋ ክብሯ በኛ ይደርብንና ህብስቱን በጻህል ወይኑን በጽዋ አድርጎ አክብሮ ለውጦ ሥጋ ወልደ እግዚአብሔር ደመ ወለደ እግዚአብሔር በሚያደርግበት ግዜ በብህንሳ ኤጲስ ቆጶስ የተሾመ አባ ሕርያቆስ በመንፈስ ቅዱስ ተገልጾለት እመቤታችንን ያመሰገነበት ምስጋና ይህ ነው:: ቁርባን ቀሳውስት ሥጋውን በጻህል ወይኑን በጽዋ አድርገው ወደ መንበር የሚያቀርቡበት አኰተት የሚለውጡት የሚያከብሩት አንድም በክብር በባለሟልነት ወደ እግዚአብሔር የሚያቀርቡ አንድም ቁርባን የሚቀበሉት የሚያቀብሉት አኰተት የሚለውጡት የሚያከብሩት ልመናው ክብሩ በኛ ይደርብንና በብህንሳ ኤጲስ ቆጶስ የተሾመ አባ ሕርያቆስ በመንፈስቅዱስ ተገልጾለት የተናገረው ቅዳሴ ይህ ነው: ጸሎታ ወበረከታ ቢል ተመስጋኝቱን ሲያይ: ክብሯ ልመናዋ ይደርብንና ጸሎቱ ወበረከቱ ቢል አመስጋኙን ሲያይ ነው::
2:- ይ:ካ: እግዚአብሔር ምስለ ኰልክሙ ቄሱ:-እግዚአብሄር በሁላችሁም አድሮባችሁ ይኑር ይበል::
ይ:ሕ: ምስለ መንፈስከ ህዝቡም እንደቃልህ ይደረግልን ይበሉ::
ይ:ካ: አእኩትዎ ለአምላክነ :-ቄሱ ፈጣርያችንን አመስግኑት ይበል
ይ:ሕ: ርቱዕ ይደሉ :- ህዝቡም ዕውነት ነው ይገባል ይበሉ
ይ:ካ: ብነ ሃበ እግዚአብሔር አምላክነ
ህዝቡም በፈጣርያችን በእግዚአብሄር ዘንድ ዋጋ አለን ይበሉ::
3:- መጽሃፍ ከመጽሃፍ ማያያዝ ልማድ ነው: አባቷ ዳዊት ለንጉሰ ሰማይ ወምድር ምስጋና ላቅርብ ባለ ግዜ ጐሥዐ ብሎ ተናግሮ ነበርና እሱም ለንግስተ ሰማይ ወምድር ምስጋና ላቅርብ ባለ ግዜ ጐሥዐ አለ አንድም ለአባቷ ለዳዊት የገለጸ መንፈስቅዱስ ምሥጢር ከምስጢር አያይዞለት ጐሥዐ አለ ወአየድዕ ይላል በልብ መደብ ቁሞ ወአነ አየድዕ ይላል በቃለ መደብ ቁሞ ልቦናዬ በጎ ነገርን አውጥቶ ተናገረ::አንድም ልቦናየ ስንቡል መንፈስቅዱስን ተቀብሎ በጎ ነገርን ገሳ ሐተታ:-በሃገራቸው የተመገቡት ምግብ ያልተስማማቸው እንደሆነ ዑድ ሰንደል የሚባል ሽቱ አለ ያንን ተመግበው በጎ በጎ ነገር ገሣው ይላሉና ያጎሥዓኒ እንዲል ትግሬ ሐተታ:- ሶስት ግዜ ጐሥዐ ጐሥዐ ጐሥዐ ብሎ መላልሶ ተናገረ ስለምን ቢሉ በንጽሃ ስጋ በንጽሃ ነፍስ በንጽሃ ልቦና መዓረግ አምሳል አንድም ወጣንያን ማዕከላውያንን ፍጹማን የሚያመሰግኗት ስለሆነ: አንድም በዚህ አለም በገነት በመንግስሠማያት ያሉ ጻድቃንየሚያመሰግኗት ስለሆነ: ከዚህስ አስቀድሞ መንግስተ ሰማይ የገባ የለም ብሎ ኋላ መንግስተ ሰማያት የሚገቡ ጻድቃን የሚያመሰግኗት ሲለሆነ: አንድም ሊቃውንት በሚስጥረ ሥላሴ መጀመር ልማዳቸው ነው: ሦስት ግዜ ደጋግሞ መናገሩ የሦስትነት: ቃሉ አለመለወጡ የአንድነት:ምሳሌ ነው:አንድም ወአነ አየድዕ ቅዳሴሃ ወአነ አየድዕ ውዳሴሃ ወአነ አየድዕ ዕበያቲሃ የሚል ነውና ሦስት አርዕስት ተናገረ ለሦስቱም ያመጣል::
4:-ወአነ አየድዕ ቅዳሴሃ ለማርያም:- አባቷ ዳዊት ወአነ አየድዕ ግብርየ ለንጉሥ ብሎ ነበርና ለዚያ ዋዌ እኔም የእመቤታችንን ምስጋና እናገራለው አለ ሐተታ:- መጀመርያ ጐሥዐ ብሎ ነበርና ለዚያ ህዳግ ይህስ ለራሱ አርእስት ነው ብሎ አለ በቅድስና ወበንጽህና ስርጉት አንቲ የሚል ነውና ለዚያ አርዕስት ነው::
አኮ በአብዝኖ በማብዛት አይደለም : አላ በአውህዶ በማሳነስ ነው እንጂ ሐተታ:-የእመቤታችን ምስጋና ከምስጋና ቢበዛ እንጂ ያንሳልን? መትህተ ፈጣሪ መልዕልተ ፍጡራን አይደለችምን ቢሉ እውነት ነው የእመቤታችን ምስጋና ሰማይና ምድር ብራና አብህርት ቀለም ዕጽው ብርዕ አዕባን መድመድ: መላዕክት ደቂቀ አዳም ጸሃፍት ቢሆኑ ባልተፈጸመም ነበር:እንደቅድስናዋ እንደንጽህናዋ አይደለም ሲል እንዲህ አለ ከዚያ ሁሉ ቅዱስ ቄርሎስ የቴዎዶስዮስን እህቶች የአርቃድያ የመሪናን ምስጋናቸውን ተናግሮ ዝውዳሴንዘተናገርነ ይውህደ እምክብርክን እንዳለ አንድም ንባብን በማብዛት ምሥጢሩን በማሳነስ አይደለም: ንባቡን በማሳነስ ምሥጢሩን በማብዛት ነው እንጂ::
ወአነ አይድዕ ውዳሴሃ ለድንግል:- እኔም የእመቤታችንን ምስጋና እናገራለው ሐተታ:-ሁለተኛ ጐሥዐ ብሎ ነበርና ለዚያ ህዳግ ይህስ ለራሱ አርእስት ነው ብሎ ኦ ድንግል አኮ ስፋጣን ዘናዘዙኪ አላ መላእክተ ሰማይ ሐወጹኪ በከመ ተብህለ ካህናት ወሊቃነ ካህናት ወደሱኪ የሚል ነውና::
አኮ በአንሆ በቃለ ዝንጋዔ:- ዝንጋዔን የሚያመጣ ዝንጋዔን የሚያስከትል ነገርን በማብዛት አይደለም: ብዙ ቢያወጉ ይዘነጉ: ብዙ ቢተቹ ይሰለቹ:እንዲሉ ነገር ከበዛ ዘንድ ከምን ተነስቶ ከዚህ ደረሰ ይባላልና ነው::
አላ በአሕፅሮ:-በማሳጠር በመጠቅለል ነው እንጂ ሲሰበር ይሰንጠር ሲረዝም ይጠር እንዲሉ:
ወአነ አየድዕ ዕበያቲሃ ለድንግል:- የድንልን ገናንነቷን እናገራለው ሐተታ:- ሦስተኛ ጐሥዐ ብሎ ነበርና ለዚያ ህዳግ ይህስ ለራሱ አርእስት ነው ብሎ ኦ ማርያም ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ ብሎ የሚያመጣ ነውና: ይህስ አይደለም አርዕስት ተቀዳደመ ለፊተኛው አርቆ ለኋለኛው አቅርቦ አይሰጥም ብሎ መጽአ ሃቤኪ ቃል ብሎ የሚያመጣ ነውና:: ወአነ አየድዕ ውዳሴሃ : ወአነ አይድዕ ቅዳሴሃ : ወአነ አይድዕ ዕበያቲሃ ብሎ ሦስት ጊዜ መላልዞ ተናገረ::
ኦ ማርያም በእንትዝ ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ ኦ ድንግል ምልዕተ ውዳሴ: ኦ ድንግል አኮ ዘተአምሪ ርስሃተ የሚል ነውና: አንድም አባቷ ዳዊት ቀደሰ ማህደሮ ልዕል:መሰረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን እስመ ሓረያ እግዚአብሄር ለጽዮን ብሎ ሦስት ግዜ መላልሶ አመስግኗታል:: ይቆየን የዚህ ክፍል ሁለት ነገ ይቀጥላል ..............ችቸር ያቆየን!!!!!

3 comments:

  1. ቃለ ህይወት ያሰማልን። እግዚአብሔር ያበረታችሁ።

    ReplyDelete
  2. አሜን:: እመቤታችን አብዝታ ትባርካችሁ::

    ReplyDelete
  3. Ye Emebetachin Bereket Behulachin layi Yider.
    Enantenim kale hiwot yasemachihu. Bertu!!!

    ReplyDelete